Tuesday, October 1, 2013

የ‘ፍም እሳቶች’ እምቢ ባይነትና ጽናት የሚያኮራን ነው ከዳኛቸው ቢያግድልኝ

ማን ነው የሚለየው? የሚደፍረው?
ይህም ትውልድ ፍም እሳት ነው።
የታለ አንድነቱ…. የፍቅር ተምሳሌቱ?
አረ ጎበዝ…..
እምቢ በል!
እምቢ…. እምቢ…እምቢ…..
የማደንቃቸው ሮቤል አባቢያ ዲሞክራሲ ከደጅ እያንኳኳ ነው በሚለው ጽሁፋቸው ዘመነኛ ቀስቃሽና ነገን አመላካች የሆኑ የዜማ ርዕሶችን እያደናነቁ የሀገራችንን ትንሳዔ ህልውና አብሳሪ የሆነውን ቀስተደመና መሰል ሰንደቅዓላማ ወጣቶች ከፍ አድርገው ስለማውለብለባቸው በውብ ብዕራቸው ከኛም አልፎ ሌሎች እንዲረዱት በእንግሊዝኛ አቅርበውት ነበር። ፕሮፌሰር አለማየሁም ይህንን ከሰጡት በላይ መልሶ ለመስጠት የተዘጋጀን አቦሸማኔ ወጣት ትውልድ አድንቀው ጽፈዋል። ልሂቃኑ ባሉት ላይ በማከል የሀገራችንን ትንሳዔ በወጣቶቻችን ለነፃነት ቀናዒነትና አልበገር ባይነት እናይ ዘንድ እውነት መሆኑን የሚያመለክት ከዘረኝነት በላይ፣ ከሀይማኖት ልዩነትም ያለፈ፣ ከፖለቲካ ድርጅቶች አጥርም የዘለለ ሀገራዊ አንድነቱን ከፍ ያደረገ ማንነትን ሲገልጹ ማየት እጅግ አኩሪ መሆኑን ደግሞ ደጋግሞ መናገር ያስደስታል።

አዛውንቱን አግልሎ ወጣቱን በሉ በሉ የሚል ወይም ወጣቱን አርክሶ ጀግና ድሮ ቀረ የሚል ዘመናትን አገናኝ የሆነውን ድልድይ አፍራሽና የትውልድን ቅብብሎሽ የሚያረክስ ሀሳብ ስሜታዊ በሆኑ ወገኖች እየተነገረ ሚዛናዊነት ሲጠፋ፣ ተስፋ ቆራጭነትም ሲስፋፋ ተመልክተን ነበር። ከወጣቶቹ አንዱ ቴዲ አፍሮ “ያለ ትናንት ዛሬ የለም።” እንዳለው መወራረስና መደጋገፍን ከፍ ማድረጉ አስፈላጊ ነው። ዛሬ ያለው እውነት ትናንት ሆኖ ባለፈው ድርጊት ላይ መሰረቱን ይጥላልና። ለዚህም ነው በትናንቱ ሁሉን አቀፍ ታሪካዊ ስህተት ተቀፍድደን፣ ዛሬን ሁሉን ነገር ተነጥቀን ላለማለፍ የትናንቱ ስህተት እንዳይደገም፣ ሸፍጥና መጠላለፍም የነገን ተስፋ እንዳያሳጣን አምቢ በል ለሚሉት ተረካቢ ወጣቶች እውቀትና ብልህነት በትግሉ ለሰነበቱ አዛውንቶችም ለብሄራዊ እርቅ ብርታትና ጥንካሬን መመኘት ተገቢ የሚሆነው።
የወጣት እድሜ ክልሉ እስከ 30 ከዘለቀ የዛሬዎቹ ወጣቶች በዚህ ምድር በተመላለሱበት ጊዜ ሁሉ ሀገራቸውን እንዲጠሉ፣ በሀገራቸውና በታሪካቸው እንዳይኮሩ የተገደዱና ሀገር ለዜጎችዋ ልትሰጥ የሚገባት ሁሉ ያልተሰጣቸው እንዲያውም ህልማቸው ስደት፣ ስኬታቸውን በግርድናና ባርነት እንዲለኩ የተገፉቱ ናቸው። የአምባገነኖች አፍራሽ ፕሮፓጋንዳ፣ ጎሰኛነትንና ጥላቻን በሚያስፋፉ ቡድኖች ሁሉ በግድ ጥላቻን በጡጦ የተጋቱት ናቸው በወጣት ቅንፍ ውስጥ ያሉትና ሀገር ከተረፈችላቸው የነገዎቹ ተረካቢዎች የሚሆኑት። ሀያ ሁለት ዐመት በአዋጅና በተግባር የተደረገው የጥላቻ ዘመቻ ሁሉ ከሽፎ ክፋትን የዘሩ ቁንጮዎቹ የሰረቁትን እንኳን ሳይበሉ በጠሉት ባንዲራ ተጠቅለው አፈር ሲረግጣቸው ወጣቱ ግን በመቃብራቸው ላይ ቆሞ ስለሀገሩ ይዘምራል፣ ስለመብቱ ይታገላል፣ ስለነፃነቱም ባደባባይ ይሰለፋል ነፍጥ አንስቶም ይፋለማል። “ማን ነው የሚለየን?” የሚለው ዘመነኛ ዜማ በቀረርቶ ታጅቦ ሲንቆረቆር ወጣቱ ከትውልድ የወረሰውንና ለትውልድ የሚያወርሰውን አጣምሮ የተቀኘው ነውና ይመስጣል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ፈጥነውና መጥቀው ዛሬን አልሰጥም ብለው ሀላፊነታቸውን ተቀብለውታል። ርዕዮት አለሙ የዚህ ምስክር ናት ወጣትነትና ሴትነት ያላገደው ኩራትና ቆራጥነትን በምትከፍለው መስዋዕትነት እያስተማረች በምትክዋ ሺህ ወጣት ሴቶች በሚያኮራ መንገድ ወደ ትግሉ እንዲቀላቀሉ አርአያ እየሆነች ነው። አንድ ርዕዮትን በምሳሌነት ስንጠራ በሺህ የሚቆጠሩ በየአደባባዩ ለነጻነት የሚጮሁ፣ በየመድረኩ ለፍትህና ለህግ የበላይነት የሚታገሉ፣ ገንዘብ ጊዜያቸውን ለመስጠት ወደሁዋላ የማይሉ በርካታ ወጣት ሴቶች በሀገርቤትና በመላው አለምም ተበትነው “ይህም ትውልድ ፍም እሳት ነው…. ኢትዮጵያዊነትን ማን ነው የሚደፍረው ማንስ ነው የሚለያየው እያሉ ነው።” እነርሱ ድምፃቸው ከፍ ብሎ በተሰማ መጠን ከፋፋዮችና አገር አፍራሾች ሲከፋፈሉና ሲፈርሱ እያየንም ነው። ኢትዮጵያዊነትን መግደል ፈጽሞ አይቻልም የወጣቱ መነሳሳት የዚህ እውነት ምስክርም ነው። አስተባባሪና መሪ ለመሆን ከመደራጀታችን በፊት ተባባሪ ለመሆን እንዘጋጅ። የትብብር ቁልፉ ከወዲያ ማዶ ያለውንም ወገን ሀሳብ መረዳትና አማካይ መንገድ መፈለጉ ነው። በመድረክ ላይና ከመድረኩ ጀርባ የሚሰራው የተለያየ ከሆነ ምንም ስም ይሰጠው ትብብሩ የእንቧይ ካብ ይሆናል። በሚናደው የእንቧይ ካብ ውስጥ መቆጠር ለአጥፊዎች ጉልበት መስጠት ብቻ ነው።
ወጣቶች በየክፍላተ ሀገራቱ እያሰሩና ሀብታቸውን እየዘረፉ መሬታቸውን እየነጠቁ ያሉትን መሳርያ አንስተው እየተፋለሙ እያገቱና እያደኑ መደፈር በቃ! መረገጥ በቃ! መገዛት በቃ! እያሉ ነው። የትግራይ ወጣቶች በስማቸው ለሚሰራው ግፍ፣ በወገኖቻቸው ዘንድ ጥላቻን፣ መጠራጠርንና መፈራራትን የሚያመጣ ለዘላቂውም በቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጥርስ እንዲነከስባቸው የሚያደርጉትን ወሮበሎች በግልጽ መቃወም፣ በነፍጥም መፋለም በመጀመራቸው ለጎጠኞቹ የትግራይ ዘራፊዎች ትግራይ መቀበርያ እንጂ መደበቂያ እንደማትሆን እያሳዩአቸው ነው። በርግጥም ኢትዮጵያውያንን በመከፋፈል ኢትዮጵያን ማፍረስ እንደማይቻል መረዳት ስለምን አዳገታቸው?
ሰሞኑን በመላው ዐለም የሚታየው ሁኔታ በምስራቅ አፍሪካ ላይ የነጻነት ጮራ እየፈነጠቀ እንደሆነ ነው። የወሮበሎቹ ተላላኪዎችና አሽከሮች በወጣት ታጋዮች መታደን ጀምረዋል፣ ይህም አስፈሪ እርምጃ ነው። በደቡብ አፍሪካ ለነጮቹ አድረው ወገኖቻቸውን የሚሰልሉና የሚገድሉትን መክረውና ገዝተውም መመለስ ያልቻሉትን እያደኑ አንገታቸው ላይ ጎማ አጥልቀው እሳት ይለቁባቸው ነበር። ያ እርምጃ ሆዳሞችን ያሸበረ ዘረኞችን ብቻቸውን ያስቀረ ነበር። የሀገራችን ፖሊሶች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላትም ከዘረኞችና ወርሮ-በላዎች ጉያ በመውጣት ወደ ሕዝቡ በመቀላቀል የሁላችንም የሆነች ኢትዮጵያን ለመመስረት የሕዝብ ወገንተኛነት ሊያሳዩ ይገባል።
ወጣቶች ትናንትን ትተው ወደፊት እየገሰገሱ ነው። ትናንት የሆነው ሁሉ ለኢትዮጵያ ሲባል የሆነ ነውና አዛውንቱ ቂም በቀልና መናቆርን፣ ከኔ በላይ ጀግናና አዋቂ የለም የሚለውን እምነትና ያልተወራረደውን ሂሳብ ለመዝጋት ተነጋግሮ ብሄራዊ እርቅንም ለማምጣት በመጀመርያ ሀገር ሊኖረን ይገባል በሚል መጠላለፉን፣ መካሰሱንና መጠራጠሩን በመተው ይህንን ሀገር ተረካቢ ወጣት ትናንት በተኬደበት መንገድ እንዳይሄድ፣ እንደ ከሸፉት አብዮቶች በደም ጎርፍ እንዳይታጠብ የመጨረሻ ሙከራ ማድረጊያው ጊዜም አሁን ነው።
በተለያየ የትግል መስክ ተሰማርተው ኢትዮጵያችንን ለመታደግ የቆረጡ ወጣቶች ተስፋን የሚያለመልሙ የሀገራችንን ሕልውናና ክብር የሚያስመልሱ ናቸው። የ’ፍም እሳቶች’ እምቢ ባይነትና ጽናት የሚያኮራንም ለዚህ ነው።
የድል ቀን እንዲፋጠን ሁላችንም እጅ ለእጅ ተያይዘን እንነሳ!
ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ በነጻነትና በክብር ለዘላለም ትኑር!

No comments:

Post a Comment